አዲስ አበባ፡- አገርን በሚያሻግረው የምክክር ኮሚሽኑ ውስጥ እንድንሰራ መካተታችን ሴቶች በወሳኝ ኃላፊነቶች ላይ ብንቀመጥ ውጤታማ መሆን እንደምንችል ዕምነት መጣሉን ያሳያል ሲሉ የአገራዊ ምክክር ኮሚሽን አባል አምባሳደር አይሮሪት መሓመድ (ዶክተር) ገለጹ።
አምባሳደር አይሮሪት መሓመድ (ዶክተር) በተለይ ለኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት እንደገለጹት፤ አገርን ያሻግራል የሚል ተስፋ የተጣለበት አገራዊ ምክክር ኮሚሽን ውስጥ ሴቶች በምክትል ኮሚሽነርነትና በአባልነትም ተካተዋል። ይህም ሴቶች በወሳኝ ኃላፊነቶች ላይ ቢመደቡ ውጤታማ መሆን ይችላሉ የሚል ዕምነት መጣሉን ያሳያል።
ሴቶች የሕብረተሰቡ ግማሽ አካል በመሆናቸው ሳናሳትፋቸው ከቀረን እንደ አገር የምናስበው ልማትና ዴሞክራሲም ሊመጣ አይችልም ያሉት አምባሳደር ዶክተር አይሮሪት፤ ይህን በማመን ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ ሴቶች በዲፕሎማሲው ዘርፍ፣ በካቢኔው እንዲሁም በተለያዩ የአመራርነት ዘርፎች ላይ እንዲመደቡ በመደረጉ የሴቶች ተሳትፎ እየጎላ መምጣቱን ገልጸዋል።
ሴቶች በትልልቅ አገራዊ ኃላፊነቶች በተለይም በአገራዊ ምክክር ኮሚሽን ውስጥ እንዲካተቱ መደረጉ የጾታ ልዩነቱ ሳይገድበን ትልቅ አስተዋጾ እንደምናበረክት እንደታመነበት ያሳያል ብለዋል።
በእኛ አገር ሴቶች ትልልቅ ኃላፊነቶች ተሰጥቷቸው በፕሬዚዳንትነት፣ በአምባሳደርነት እንዲሁም በአገራዊ ምክክር ኮሚሽኑና በተለያዩ የኃላፊነት ቦታዎች ላይ መቀመጣቸው ለሌሎቹም እንስቶች የሚያስተላልፈው መልዕክት አለ። በዋናነትም ሴቶች ኃላፊነት ቦታ ላይ ቢመደቡ የሚጠበቅባቸውን መወጣት እንደሚችሉ ለሕብረተሰቡ ተገቢውን ትምህርት ለመስጠት ይረዳል ሲሉ ተናግረዋል።
አምባሳደር ዶክተር አይሮሪት ከሆነ፤ ሴቶች በኃላፊነት ደረጃ ሲሳተፉ ከታች ላሉ ታዳጊ ሴቶችም እንደ ጥሩ ምሳሌ መሆን ይችላሉ። በመሆኑም ይህን ልምድ አጠናክሮ መቀጠል ይገባል። ሴት ልጅ በተፈጥሮ የተለያዩ ኃላፊነትን በብቃት የመወጣት አቅም አላት ያሉት አምባሳደር ዶክተር አይሮሪት፤ ብዙ ውጣ ውረዶችም ቢኖሩም ነገን በማለም ችግሮችን እየተወጡ ለአገር የሚጠቅም ትልቅ ደረጃ ላይ እንደሚደረስ ለዚህም ምሳሌ የሚሆኑ በአገራችን በርካታ ሴቶች መኖራቸውን ተናግረዋል።
ዋናው ነገር ግን የባሕልና የአስተሳሰብ ተጽዕኖዎችን እያለፉ ወደተሻለ ደረጃ መድረስ ነው። እኔም እንደ አንድ ሴት የሚያጋጥሙትን ተጽዕኖዎች አልፌ ነው ለዚህ ደረጃ የበቃሁት። በመሆኑም ወጣት ሴቶች የሚፈልጉበት አላማ ለመድረስ ተስፋ ሳይቆርጡ ጥረት ማድረግ ይኖርባቸዋል ብለዋል።
ለአገራዊ የምክክር ኮሚሽኑ አባልነት መመረጤ ትልቅ ኃላፊነትና አደራ ጭምር በመሆኑ አገሬን ለማገልገል በመቻሌ ደስታ ይሰማኛል ያሉት አምባሳደር ዶክተር አይሮሪት፤ ይህንን የሕዝብ አደራ በታማኝነትና በቅንነት ለመወጣት ዝግጁ ነኝ ሲሉ ተናግረዋል።
በአገራዊ ምክክሩ መድረኮች ላይ ሊንጸባረቁ በሚችሉ የተለያዩ አስተሳሰቦች ላይ ምንም አይነት አድሎ ሳላደርግ አገሬን ለማገልገል ያለኝ ቆራጥነትም ከፍተኛ ነው ብለዋል።
በተለያዩ ቦታዎች በሚፈጠሩ ግጭቶች ዋነኛ ተጠቂዎቹ ሴቶችና ሕፃናት ናቸው ያሉት የኮሚሽኑ አባል፤ የችግሩ ዋነኛ ተጠቂ የሆኑትን ሴቶች በግጭት አፈታቱ ስርዓት እንዲሳተፉ መደረጉ ደግሞ ለውጤታማነቱ አይነተኛ ጥቅም ይኖረዋል ሲሉ ተናግረዋል።
የሃይማኖት አባቶች፣የፖለቲካ ፓርቲዎች እንዲሁም ሁሉም የሕብረተሰብ ክፍልም በምክክሩ ላይ በመካፈልና አስተያየቱን በነጻነት በመስጠት ንቁ ተሳትፎ እንደሚያደርግ ይጠበቃል። ሴቶችም አገራዊ ፖለቲካዊ ጉዳዮች ላይ ያላቸውን ተሳትፎ ለማሳደግ መድረኩን በአግባቡ ሊጠቀሙበት ይገባል ሲሉ መልዕክት አስተላልፈዋል።
መላው ኢትዮጵያዊም ከኮሚሽኑ ጎን በመሆን ድጋፍ እንዲያደርግና የሚጠበቀው አገራዊ መግባባት ውጤት እንዲያገኝ የበኩሉን አስተዋጽኦ እንዲያደርግ አምባሳደር ዶክተር አይሮሪት ጥሪ አቅርበዋል።
መዓዛ ማሞ
አዲስ ዘመን የካቲት 29 /2014