አዲስ አበባ፡- ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቶችን ጨምሮ ወቅቱን ጠብቀው የግዥ እቅድ ያላቀረቡ 60 የፌዴራል ተቋማት ጉዳያቸውን ለገንዘብ ሚኒስቴርና ለፓርላማ ሊያቀርብ መሆኑን የመንግሥት ግዥና ንብረት ባለስልጣን አስታወቀ። የተቋማቱ ሥም ዝርዝርም በሚዲያ በኩል ይፋ ሊደረግ እንደሚችልም ተጠቁሟል።
የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር አቶ ሃጂ ኢብሳ በተለይም ለኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት እንዳስታወቁት፤ ተቋማት የግዥ እቅዳቸውን ማቅረብ ያለባቸው በበጀት ዓመቱ መጀመሪያ ቢሆንም የበጀት ዓመቱ ሩብ ዓመት ተጠናቆም ማቅረብ አልቻሉም ብለዋል። ከእነዚህ የፌዴራል ተቋማት መካከል ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቶች እንደሚገኙበት ተናግረዋል።
በአሁኑ ወቅት 169 ከሚሆኑ የፌዴራል ተቋማት ውስጥ 60 የሚሆኑት የፌዴራል ተቋማት የግዥ እቅድ አላቀረቡም። አሁን የበጀት ዓመቱን ሩብ ዓመት አጠናቀናል። ሕጉ የሚለው ደግሞ ቀድማችሁ እስከ ሐምሌ 30 አሳውቁ ይላል ሲሉም ተናግረዋል።
የሕዝብ እንደራሴዎች የአገሪቱን በጀት ካፀደቀ በኋላ ተቋማት እቅዳቸውን ከልሰው ይልካሉ። ልክ ይህ በጀት እንደተፈቀደ ተቋማት የግዥ እቅድ ማዘጋጀት አለባቸው ያሉት አቶ ሐጂ፤ ነገር ግን ብዙ ተቋማት ብድግ ብለው የግዥ እቅድ ያቀርባሉ። ዓመቱን ሙሉ ቁጭ ብለው በመጨረሻ አካባቢ ከፍተኛ ግዥ የሚያቀርብበት ምክንያትም አንዱ በዚህ የተነሳ ነው። በዚህ ወቅት ደግሞ ወደ ጨረታ አይሄድም፤ ወደ ልዩ የግዥ ፈቃድና ውስን ጨረታ፣ ለአንዱ ቀጥታ መስጠት ወደሚለው ይሄዳል። አልፎ አልፎ የተወሰኑ ተቋማት ደግሞ እቅዳቸው እና ሥራቸው ተናቦ የሚሄዱ አሉ። በርካታ ተቋማት ግዥ የሚያካሂዱት፣ ስልጠና የሚሰጡት በዓመቱ መጨረሻ ነው። ይህ የሚሆነው ለምንድን ነው ሲሉም ጠይቀዋል።
‹‹አንዳንድ ተቋማትም ስልጠና የሚሰጡት ዓመቱን ሙሉ ቁጭ ብለው ግንቦት ላይ ነው። ይህ ዓላማ ቢስ፣ የባከነ፣ የሌብነትና ገንዘብ እንዳይተርፍ የሚሰጥ ስልጠና ነው። ማሰልጠን ካለብንና መጠናቀቅ ያለባቸው በመጀመሪያው ሩብ ዓመት የዝግጅት ምዕራፍ ወቅት መሆን አለበት›› ብለዋል።
«እኛ የመጀመሪያው ሩብ ዓመት ስልጠና እንሰጣለን። በሁለተኛው ሩብ ዓመት የሰጠነው ስልጠና ውጤት ማምጣት መቻሉን ወጥተን ግምገማ እናደርጋለን። ሙስና መቀነስ አለመቀነሱን፣ የግዥ እቅድ መኖር አለመኖሩን እናያለን። እኛ ዘንድ የግዥ እቅድ የሌለው አካል አይስተናገድም። የገንዘብ ሚኒስቴር በጀታቸውን ሊለቅ ይችላል። አሁን ግን ደብዳቤ አዘጋጅተን እያሰራጨን ነው። ለፓርላማ፣ ለገንዘብ ሚኒስቴር የግዥ እቅድ የሌላቸው ስለሆነ በጀታቸውን ያለአግባብ የሚጠቀሙ ተቋማት ብለን እናሳውቃለን» ብለዋል።
ክፍለዮሐንስ አንበርብር
አዲስ ዘመን ጥቅምት 5 ቀን 2015 ዓም